Showing posts with label Literature. Show all posts
Showing posts with label Literature. Show all posts

Monday, November 9, 2015

ያንድ ሰንጋ ትርጉም በሁለት ልኳንዳ ቤቶች ካራ

.
ይኽ በስዕሉ ላይ የምትመለከቱት የስጋ ተራራ የተሰኘ ሰንጋ የትውልድ መንደሩ ከወደ ሐረር ነው፡፡ አሳዳጊው ሐረር ውስጥ የምትገኝ አንድ የገጠር ቀበሌ መስጂድ ሼህ የሆኑት ሀጂ እንድሪስ ናቸው፡፡የዚህ መልከኛ ሻኛም ሰንጋ የዘር ሀረግ ሲመዘዝ እንደሚከተለው ነው፡፡የእናቱ የትውልድ ሀረግ የከብት አርቢ ከሆነው ስመጥር የአፋር ክልል ተወላጅ ከብቶች ዘር ግንድ ከሆኑትና የወተት ምንጭ እየተባሉ ከሚንቆለጳጰሱት ያርብቶ አደር ከብቶች ወገን ናት፡፡
 

አባቱ በመንደሪቷ ውስጥ አለ የሚባል የከብት በረት እየገለበጠ የመንደሪቷን ልጃገረድና ድርስ ጊደሮች ሚደፍር ሽንጣምና ቁመተ መለሎው፤ አሳዳጊው ቄስ ሞገሴ አፄ-በጉልበቱ እያሉ ሚጠሩት ኮርማ ነው፡፡ አባቱ አፄ-በጉልበቱ መንደሬው ዘሩን ፍለጋ ሰርክ ድርስ ጊደሩን እየያዘ ቄስ ሞገሴን ደጅ ሚጠናለት፤በቀን ከሶስት ያላነሱ ጊደሮችን አንገት ጠምዘው በግድ ሲያስጠቁት ደከመኝ የማያውቅ ወስዋሽ ጀግና ኮርማ ነበር፡፡አብዛኞቹ የመንደሪቷ ላምና ሰንጋዎች የዚሁ በውድም በግድም ጊደሮች ላይ ጥቃት አድራሽ የሆነው(አጥቂው) አፄ-በጉልበቱ የተሰኘው አባቱ አብራክ ክፋይ ናቸው በዚህም ካብዛኛው የመንደሪቷ ከብቶች ጋር የስጋ ዝምድና አለው ያባት ወገን እህትና ወንድሞቹ ናቸው፡፡
ቄስ ሞገሴና ሀጂ እንድሪስም ቢሆኑ ካንድ መንደር ኗሪነታቸውም ባለፈ ካንድ ሸንጎ የሚቀመጡ፣የተጣላን የሚያስታርቁ ሀገር ሚያከብራቸው ሽማግሎችና የልብ ወዳጅም ናቸው፡፡ ሀጂ እንድሪስ የግተ ለምለም ዘር የሆነችው ጊደራቸው ላቅመ ግንኙነት ደርሳ ኖሮ እብልቷ ፍም ሲመስል የታሰረችበትን ገመድ ልትበጥስ በረቱን እያመሰች ብታስቸግራቸው...እምቧ!!... እምቧ!! እያለች... በምቧቧ ከረዮዋ እረፍት ብትነሳቸው ረመዳን በወጣ በሳምንቱ ባንዱ ለት ማልደው ቄስ ሞገሴ ጋር ይዘዋት ሄደው ለቀበኛው ኮርማ አፄ-በጉልበቱ ቁርስ አስደረጓት፡፡ ይኽ ስጋም የስጋ ተራራ ለመባል የበቃው ሰንጋም ያን ዕለት ተፀነሰ፡፡
ገና በናቱ ማህፀን እያለ ያለቅጥ እድገት ያመጣው ፅንስ እናቱ በርግዝና ዘመኗ ከቦታ ወደ ቦታ እንዳትንቀሳቀስ ከልክሏት ባለቤቱንም ሆነ መንደርተኛውን ስጋት ውስጥ ጥሎ ነበር፡፡የናቱ የርጉዝ ሆዷ አወጣጠር ከመንታም በላይ እንደያዘች ያያት ሰው ሁሉ ጥርጣሬ አልነበረውም፡፡ግዜው ደርሶ ከረጅም ምጥ በኋላ ጥጃው ሲወለድ ግን መንደርተኛው እንዳሰበው መንቶች ሆነው አልተገኙም፡፡ ይልቁንም ገና በማለዳው የስጋ ሰንጋነቱ ውልውል ውስጥ የማይገባው አንዱ ጥጃ የሁለት ጥጆችን ግዝፈት የያዘ ጥጃ ሆኖ ተወለደ እንጂ፡፡የዚህን ገዛፋ ጥጃ መወለድ ዜናን፤ሀጂ እንድሪስ በወተት እንደምታራጫቸው ተስፋ የጣሉባት ዘረ ግተ ለምለም ጊደራቸው በሰላም መገላገሏን የሰማ ሀገሬ ሁላ ባገሩ ደንብ መሰረት የእንኳን ደስ አሎት ምኞቱን አጎረፈላቸው፡፡
ሀጂ እንድሪስም የወተት ጌታ ለመሆን ያበቃቸውን አላህ በደስታ ተሞልተው አመሰገኑ ላዲስ ውልድ ጥጃቸውም የስጋ ተራራ ሲሉ ስም አወጡለት፡፡ ከልጅነት እስከ ወይፈንነት ሲለጥቅም ላቅመ ሰንጋነት እስከበቃበት ዕድሜው ድረስ እንደ ስሙ የስጋ ተራራ እስኪያክል እየቀለቡ አሳደጉት፡፡የዚህ የስጋ ተራራ የሚመስል ሰንጋ ታሪክም ከሀረር እየተሳበ አዲስ አበቤውን በሞንሟና ስጋ አቅርቦታቸው ጉድ የሚያስብሉት ልኳንዳ አራጆች እነ ጭንቅሎ፣ ጊርጊሮና ቢላል ጆሮ ደረሰ፡፡
የበሬ ነጋዴው፣የደላላው፣የባለልኳንዳው ካልሽጡልን ውትወታ ሀጂ እንድሪስን መቀመጫ ነሳቸው፡፡ መጀመሪያ ሰሞን በእንቢታቸው ቢፀኑም “ድሮስ ገበሬ ከብት ሚያረባና ሚያደልብ ሁነኛ ጥቅም ሊያገኝበት እንጂ እበረት አጉረው አይን-አይኑን ቢያዩት ምን ዋጋ አለው!!...ደግሞም አላህ በስተርጅናዎ ደጅዎ ድረስ ያመጣሎትን እርዝቅ(አዱኛ) መግፋት ጡር አለው፡፡አላህ ክፉውን ያርቅልዎ እንጂ እንኳን የከብት የሰው ቋሚ እንደሌለው መቼም እኛ ለርስዎ አንነግሮትም፡፡ ይሄን የመሰለ የስጋ ዳሽን በከብት በሽታ ፍግም ያለ ለት ኋላ የሚተርፍዎ ፀፀት ነው” እያለ ጎረቤት መንደሩ ከምክር ደብልቆ ፍርሃት ቢነዛባቸው ነገሩን አጢነው ለፉክክር ከቀረቡ ተጫራች ልኳንደኞች አንዱ ከቃላቸው አይወጡም ለሚባሉት የልብ ወዳጃቸው እጅ መንሻ ሰጥቶ ላስጀነጀናቸው ለሳቸውም አይናቸውን ማያሹበት ዋጋ አቅርቦ ልባቸውን ላማለለው ለክርስቲያን አራጁ ጊርጊሮ ፤ እንዲሁም አንዱን ከስጋ ተራራው መለስ ያለውን ሌላ ሰንጋቸውን ደግሞ “ይኼን የስጋ ተራራ ለሌላ ሰው አሳልፈው ከሰጡ ወላሂ እቀየሞታለሁ” እያለ ለሞገታቸው ቢላል “አላህ ስጋውን ይባርክላችሁ!!” ብለው መርቀው ሸጡላቸው፡
 መቼም ሰንጋ በቁሙ እያለ ክርስቲያንም ይሁን እስላም ቤት ይደግ ሀይማኖት የለውም፡፡ሰንጋ በቁሙ እያለ ባርባ ቀኑ ክርስትና ተነስቶ ክርስቲያን ሰንጋ ተብሎ ባንገት ክሩ አይለይ?!... አሊያም ባሳዳጊ በባለቤቱ ሐይማኖት ህግ መሰረት ሰልሞ እስላም ሰንጋ ተብሎ መለያ ቆብ አይደፋ?!...መቼም ሰንጋ በቁሙ እያለ እስላሙ ለክርስቲያኑ ፤ክርስቲያኑ ለእስላሙ አልሸጥልህም፣አልገዛህም ላይባባሉ ነገር...
በሞቱ፤ባንገቱ የተሳለ ካራ ካሳረፉ በኋላ ወርችና ዳቢቱን...ሽንጥና ሻኛውን...ታላቅና ታናሹን ...ምላስና ሰንበሩን...ጎድንና ቅልጥሙን...ጉበትና ኩላሊቱን... በካራ ክርስትና ማንሳት፤ባራጁ ካራ ማስለም... ከገደሉ በኋላ ስጋውን ለገዛ ሃሳባችን...በቁሙ ቁልቢን ብለን የሸጥነውን፤ወላሂ ብለን የገዛነውን ሰንጋ ከጣልነው፣ከገፈፍነው፣ከበለትነው በኋላ ብንለያይበት፣የሚበላውን ከወዳቂው አካሉ ነጥለን ...ስጋውን ከቀንድ ና ቆዳው ለይቶ የሚያናጅስ ሐይማኖታዊ የቢስሚላሂና የበስመ-አብ ፅንሰ ሐሳብ፤ያንድ ሰንጋ ትርጉም በሁለት ልኳንዳ ቤቶች ካራ ልዩነት፣በአራጁ ምናባዊ መነባንብ…አራጁ ካራውን በሬው አንገት ላይ በሚሽጥበት ትርጉም የለሽ አቅጣጫ፤በሬውን ለመጣል እኛ በፈጠርነው የሀሳብ ዞን፤ወደ መካ፣ ወደ ምስራቅ አውድቀን በንሰሳው ውድቀትና አወዳደቅ ሃላል፣የተባረከ እያልን በከንቱ ሰዋዊ ሀሳባችን መዋደቅ ትርጉም የለሽ ይሆንብኛል...
የቀንድ ዋንጫውን፣ከቆዳው የተበጀውን ጫማና፣የቆዳ ልብስ ያለልዩነት እየተጠቀምን በስጋው መለያየት የፈለግንበት የክፋት ምርጫችን ሰማያዊነት፣ጀነታዊነት አልታይህ ይለኛል...የሐይማኖትና ሐይማኖተኞች አስተምህሮ ከፍቅርና አብሮነት ይልቅ ለልዩነት ያላቸውን የፀና አቋም አስረጂ ይመስለኛል፡፡ አባ ለሚካዔል ያመት ንግስ ለት ለቅዳሴ ከቤትዋ ሲወጡ ያረጉት መጫሚያዎ ሲረግጡት ቢስሚላሂ!!...ቢስሚላሂ!!...ያ-አላህ!!..ያ-አላህ!! ይላል…ምነው የእስላምና ክርስቲያን ስጋ ሲለዩ …የእስላምና ክርስቲያን ቆዳ መለየት ተሳንዎ?!... ሀጂ ለጁምዓ ለት ስግደት ሲሄዱ ያረጉት መጫሚያዎ ሲረግጡት በስማብ-በወልድ!!...በስማብ-በወልድ!!...ምነው በድንግሊቷ?!...ምነው በኡራኤል!!...ይላል እርስዎስ ቢሆኑ ምነው የእስላምና ክርስቲያን ስጋ ሲለዩ …የእስላምና ክርስቲያን  ቆዳ መለየት ተሳንዎ?!...


ይህቺን ሊንክ ከልከው https://www.facebook.com/kindeta ዘለቅ ብለው ያንብቡኝ!!... እርሶም የመውደጃ ምልክተዋን ተጭነው መውደድ- መዋደድዎን አይርሱ?! ለወዳጅዎም ግብዣ ይላኩ፡፡

Thursday, October 29, 2015

ጭን-ገረድነት፣ውሽምነትናቅምጥነት ባለትንሳዔው ትውፊታችን


#ክንዴነህ ታመነ #Kindeneh Tamene

እንዴት ከረማችሁማ ብዬ ጥሁፌን ልጀምራት አልኩና የኤፍሬም እንዳለ ወግ ልትሆንብኝ ሆነ…የቀኑ ደመናማነት ሀገሩን የጥጥ ማሳ አስመስሎታል….ሰማዩ በተራው ጭጋጋማ ቀለም የተቀባ የሰዓሊ ሸራ ይመስላል… ፀሐይት እንደ አብዮት ልጆቿን ቀርጥፋ ልትበላ አደባባይ የወጣች ነፍጠኛ ትመስላለች ብዬ ልጀምር አሰብኩና በዕውቀቱ ስዩም በሀገራችን ድርሰት ፅሁፎች መቼት ገለጻ ላይ  ያፌዘባት ጥሁፉ ትዝ ብትለኝ … ጥሁፌን እንዴት ብዬ ልጀምራት ይሆን ሀሳብ ተቸንክሬ ሰዐታት ነጎዱ…ኤዲያ ደግሞ እንዴት ልጀምር ብሎ በሃሳብ መንፏቀቅ ምን ይሉት ጅልነት ነው ብዬ ወዲያ ትቼው ልነሳ ሲዳዳኝ አንድ መላ ተዘየደችልኝ…እኔ እስከማውቀው ከሀገራችን ጠሀፍት ውስጥ ጥሁፉን በመፈክር የጀመረ ጠሀፊ ያለም አይመስለኝ …እቺ ያልተበላባት የጥሁፍ መጀመሪያ ስልት ናት…ፈክሮ መጀመር ልዩ ብልሀት ናት…እንግዲህ ግራ እጃችሁን እያነሳችሁ አብረን እንፈክራለን…ዳይ ወደ ፍከራችን !!
የነገደ ሰለሞን ስርወ መንግስታት ያወረሱን የነቃ ማህበረሰብ መለያ የሆነው የጭን-ገረድነት ባህላችንን ጠብቀን ለተተኪው ትውልድ እናስረክባለን!!
ፖለቲካዊ ውሽምነት ለህዳሴያችን መረጋገጥ ዋስትና ነው!!
ህዝባዊ ቅምጥነት የልማታችን ማሳለጫና ሀገራችንን ከፀረ-ልማት ኃይሎች ምንታደግበት የተባበረ ክንዳችን መገለጫ ነው!!
ጭን-ገረድነት፣ውሽምነትና ቅምጥነት ሰፊው ህዝባችን በሀገሩ ፖለቲካ  ውስጥ ያለውን ተሳትፎ የሚያረጋግጥበት የተሞክሮ መድረክ ይሆናል !!
አሁን ከፍከራ ብዛት የዛለ ክንዳችንን ለልማታዊ ሐሳባችን እናውለው፡፡ከዚህ ቀደም  “የአይጦች ግልቢያ” ወይም “ራት ሬስ” ብዬ የጣፍኳትን ጥሁፍ ያነበባችሁ ሰዎች ምን ይዘባርቃል እንዳትሉ በቀደመው ፅሁፌ ለማንሳት የወደድኩት ሃሳብ በሀገራችን ፖለቲካ ውስጥ በተቃውሞ አሊያም ፅንፍ በያዘ ዘርና ዘረኝነትን መሰረት ባደረገ የፖለቲካ አጀንዳቸው ጎራ የለዩ ወገኖችና እንዲሁም (የገዢው ፓርቲ ልሂቃን እንደሚሉት ፖለቲካ ሐይማኖት አይደለም፤ማንኛውም ጥቅሙ የተከበረለት አካል የፓርቲው የተባበረ የኃይል ክንድና የአውራ(ሬ) ፓርቲው ቀጣይ ህልውና መሰረት ይሆናል በሚል ፍልስፍናና ፖለቲካዊ ብልጠት ከጊዜና ከወቅት ጋር እየተሰናሰለ በሚቀረፅ ፖለቲካዊ ስትራቴጂ  ለአዳዲስ አባላት ምልመላ ፓርቲው ከሚሠጠው ትኩረት በላይ የተወሰነ የህብረተሰብ ክፍልን የጥቅም ተጋሪ በማድረግ ጊዜያዊ ጥቅሙ የተከበረለት በጥቅም የታወረ  ጭፍን ደጋፊ የማበራከት ፖለቲካዊ መሰሪነት ተጋላጭ(ቨልነራበል)የሆነው ክፍልና በጭፍን ደጋፊነት  ጎራ የተሰለፈው ወገንና  የተቃውሞ  ፖለቲካዊ የትግል ጎራ የተበጣጠሰና ከሚያቀራርበው ነገር ይልቅ የሚያራርቅ የብሄርተኝነት አጀንዳቸው  ለገዢው ፓርቲ ዕድሜ ማራዘሚያነት የተቀመመ የዘር ፖለቲካ መርዘኛ  እሳቤ የማስፈፀም አይጣዊ ሚናቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ለማሣየት ያሰበ ነበር፡፡የዚህን ጥሁፍ ሙሉ ሃሳብ ማንበብ ከፈለጉ ወረድ ብለው ገፄን ይመልከቱ፡፡
ለዚህ ፅሁፌ መነሻ የሆነኝ ከአበዋዊ ብሂል፣ባህል ጋር የተሰናሰለ ዘመናዊነት እና ቇቅነት የወለደው ፋሽን አሊያም የመተጣጠፍ አኗኗር ዘይቤ፤ ያባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ ጭን-ገረዳዊ ፖለቲካዊ ማንነት፤እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው ባይ ውሽማዊ ኢትዮጵያዊ ጠባይ፣ወይ ካለው ተወለድ ወይ ካለው ተጠጋ ሀገርኛ የቅምጥነት አመለካከት ሰዋዊ ስብዕናን ሽባ አድርጎ የሚያስቀር የአመለካከት ልምሻነት ከትውፊት፣ከባህል፣ከሐይማኖት እና ፖለቲካዊ ስርአቶች ጋር ያላቸውን ቁርኝትና የዛሬው ጉራማይሌ ሀገራዊ አመለካከታችን ሰበበ መንስዔ  ይሆናል ያልኩትን ግላዊ ምልከታዬን ማቋደስ ነው፡፡በኔ እምነት ፅንፍ የያዙ ድጋፍና ተቃውሞ ፖለቲካዊ አመለካከቶች ከነጉድፋቸው በምንም መስፈርት ከላይ ካነሳሁት የአመለካከት ልምሻነት ጋር  ለንፅፅር እሚቀርቡ አይደሉም፡፡የሰው ልጅ ለሚያምንበት ነገር፣ለሚያምንበት ዕውነት መቆሙ የሰውነቱ መገለጫ ነው፡፡ዕውነቱና ዕምነቱ እንዲሁም የቆመለት ዓላማ ሀገርና ወገንን ታሳቢ ያደረገ ነው?...የሰፊውን ህዝብ የባህል፣የሐይማኖት፣የብሔር ነፃነት አስጠብቆ ሀገርን በጋራና ባንድነት ሚያራምድ  ነው ዓላማው?በሚለው ጉዳይ ላይ ያለን ልዩነት እንደተጠበቀ ሆኖ
በግሌ የትኛውም ግለሰብ ሆነ ቡድን ቆሜለታለሁ የሚለው ፖለቲካዊ አላማ ቅዱስ አሊያም እርኩስ ነው ብለን እምናወድስበትና እምንኮንንበት ሁላችንንም ሊያስማማ የሚችል መስፈሪያ ባይኖረም…ግለሰቡ ወይም ቡድኑ የያዘው መስመር ሰይጣናዊ ይሁን መላዕካዊ፣ቅዱስም ይሁን እርኩስ ፣አጥፊም ሆነ አልሚ ቢያንስ የቆመለት፣የሚቆምለት ዓላማ አለው፤ቢያንስ የሚገድልበትና የሚሞትለት ምክንያት አለው፡፡በተመሳሳይ ከጭፍን ጥላቻና ከጭፍን ደጋፊነት የራቀ በአመክንዮ ነገሮችን የሚመረምር አድማጭ ያጣ በሀገሬ ጉዳይ ላይ ያገባኛል የሚል ሐቀኛ ሀገር ወዳድ የሆነ ኢትዮጵያዊ  ውስን ቢሆንም መኖሩ የማይካድ ነው፡፡ዛሬ ላይ ግን ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት የጭን-ገረድ፣የውሽማና የቅምጥ  ፖለቲካዊ ስብዕናና ማንነት ያዳበሩ ሰዎች ምድር ሆናለች፡፡
በዚህ ጥሁፍ ቀጣይ ክፍል  ከላይ በርዕሱ የተመለከትነው በቀደመው ስርዓት ነገስታትና ባላባቶች  በሀይማኖታዊ መሰረት ላይ የገነቡት  ማህበረሰባዊና ፖለቲካዊ ስብዕናና ኢትዮጵያዊነት ከነገስታቱ ወሲባዊ ጠባይ ጋር እንዲመቻመች ያደረጉት የጭን-ገረድነት፣ውሽምነትና ቅምጥነት ዐመል በግዜ ሂደት ባህላዊ መሰረት መያዙና በተራው ማህበረሰብ ሳይቀር እንደ ትከክል ተወስዶ ተቀባይነት አግኝቶ ማህበረሰባዊ ወሲባዊ ጠባይ ለመሆን የበቃው በአዝማሪ ዜማና ግጥም ሳይቀር ባል በሚስቱ ላይ፣ሚስት በባሏ ላይ መወሸም፤በሚስት ላይ ቅምጥ ማኖር የወንድነት መገለጫ ተደርጎ ለውዳሴ የሚያበቃ መልከጥፉን በስም ይደግፉ አይነት ማህበረሰባዊ ነውር“እዚህ ጋር እኔ ነውር የሚለውን ቃል ለመግለፅ የተጠቀምኩት ድርጊቱን በመሰረታዊነት የክርስትና እምነት ተከታዩ  ማህበረሰብ ከምንም በላይ በሚያምናቸው የክርስትና መምህሮቹ ሐይማኖታዊ አስተምሮዎች  ጋር ድርጊቱ የሚጣረስና ባንድ በኩል እራሱም ነውር  ብሎ ስለሚኮንነው ነው፡፡
በሌላ በኩል የጋብቻን ቅዱስነት፣አንድ ወንድ ለአንድ ሴት መፅሐፍ ቅዱሳዊ አስተምሮ፤ በአይኑ አይቶ በልቡ የተመኘ አመነዘረ የሚለውን ከአስርቱ ትዕዛዛት አንዱ የሆነውን ሀይማኖታዊ ቀኖናና  የዕምነት ድንጋጌ ጋር በፍፁም የሚቃረነው “ከዝሙት የሚቆጠረውን ኩነኔያዊ ተግባር”በባህልና  በፖለቲካዊ ትክክለኝነት ሂሳብ  ሁለት ፍፁም ሊጣጣሙና በአንድ ሐይማኖታዊ አስተምሮ የተቃኘ ስብዕና ውስጥ ተቻችለው ሊገኙ የማይችሉ፤ሁለት ፅንፍ የያዙ አመለካከቶችን አንድ ማንነት ሊቀበላቸውና ሊተገብራቸው የሚከብዱ መንታ ጠባያት እርስ በርሳቸው በሚጣሉ ማቶ ተረቶች እያስታከከ ከትውልድ ትውልድ እየተላለፈ የመጣ አበዋዊ ባህልና ሐይማኖትን የቀየጠ በሁለት ቢላ የመብላት፤ባንድ ራስ ሁለት ምላስ አመለካከት ለዛሬው የተምታታ ኢትዮጵያዊ ስብዕና፣ማንነት መሰረት ነው ባይ ነኝ፡፡እርግጠኛ ባልሆንም ስለዚህ ሀገራዊ ፖለቲካዊ ስብዕና ሌሊሳ ግርማ የሚባል ጠሀፊ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ የጣፈውን መጣጥፍ ያነበብኩ ይመስለኛል፡፡
ትክክልና ስህተት ብሎ እራሱ የፈረጃቸውን ሁለት አብሮ አይሄዴ አመለካከቶችን በእኩል ተቀብሎ የሚኖር ሁለቱንም እያጣቀሰ ልቡን ለእግዘኤር ጭኑን ለሰይጣን ሚገብር፣ሰይጣንን ባደደባባይ የሚኮንንና የሚያብጠለጥል በጓዳው ሰይጣንን የሚያከብር ማህበረሰብ፣ሲያሻው ባደደባባይ ሙስናና ሙሰኞችን የሚጠየፍ፣ሌባ እጅ ከፍንጅ ያዝኩ ብሎ ተባብሮ እንደ እባብ ጭንቅል ጭንቅሉን  የሚቀጠቅጥ በሌላ በኩል እከሌ ከመንግስት ካዝና ይኼን ያህል ሚሊየን ብር ሰረቀ ሲባል እንዲህ ነው እንጂ እናቱ የወለደችው እያለ የሚያሞካሽ፤ለአፉ ሌብነትን የሚጠየፍ  በልቡና በተግባሩ ግን ሌቦችን የሚያደንቅ፣ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል እያለ ሚተርትና ስትሾም ካልበላህ ከንቱ ነህ እያለ ሚያጀግን፤ እርስ በርሱ የሚጣረስ  አንዱ ሌላውን ደግፎ ሊቆም በማይችል አመክንዬ በጎውን ከክፉው ያዳቀለ ድቅል ኢትዮጵያዊ ማንነት፣ክልስ ኢትዮጵያዊ ማንነት ውዥንብራችንን መለስ ብለን ብንቃኘው ምን ይለናል፡፡ከዚህ በመለስ አለማየሁ ገላጋይ በወሬሳ ልቦለዱ ተረታችንና የተምታታ ስብዕናችን ዋዘኝነት ጋር አዋህዶ ሊያሳየን የፈለገው ይሄንኑ መለቲፕል ፐርሰናሊቲ የተጠናወተው ጠባያችን ይመስለኛል፡፡
ይህቺን ሊንክ ከልከው https://www.facebook.com/kindeta ዘለቅ ብለው ያንብቡኝ!!... እርሶም የመውደጃ ምልክተዋን ተጭነው መውደድ- መዋደድዎን አይርሱ?! ለወዳጅዎም ግብዣ ይላኩ፡፡

Sunday, October 4, 2015

የአይጦች ግልቢያ (Rat-Race



የዘር (የብሔር) ፖለቲካ አቀንቃኞች የአንድን ብሔር ማንነት ከሚኖርበት ቦታ (ጂኦግራፊ) ጋር ብቻ የሚያያዙበት አመለካከት አንድምታው ብልጠት የተሞላበት የፖለቲካ ጨዋታ ነው፡፡በጫወታውም የጫወታው ፈጣሪዎች ቀመራቸው ያለ ምንም እንከን ላስፈፃሚነት አስቀድመው በታጩት ዐይጦች ተግባራዊ እየሆነላቸውም ነው፡፡ 
የዚህ ፖለቲካዊ ጫወታ እሳቤም ሆነ የተጫዋቾቹ አይጦች ተግባር ሮበርት ቲ.ኪዮሳኪ የተባለው አሜሪካዊ ባለፀጋ በአለማችን ላይ ያሉ ባለፀጎችና ድሆች መካከል ያለውን ፤ ገንዘብ ባላቸውና በሌላቸው ሰዎች መካከል እየሰፋ የመጣውን ቅጥ የለሽ የሀብት ልዩነት መሰረት ላይ ያተኮረው “ ካሽ ፍሎው” የተሰኘ የሰሌዳ ላይ ጌም አሊያም “ራት ሬስ” ብሎ ከሚጠራው ጫወታ ጋር በብዙ መልኩ ይመሳሰልብኛል፡፡ 
ምክንያቱም ባንድም ሆነ በሌላ መልኩ ከኢህአዴግ ጋር ባንድነት የተሰለፉም ሆነ በአክራሪ የዘረኝነት አመለካከታቸው በተፃራሪ ሀይልነት የተሰለፉ ግለሰቦችም ሆነ ቡድኖች የዚህ የአይጦች ግልቢያ ውድድር ጫወታ አካል ናቸው፡፡ለዚህ ክፋት ወለድ ፖለቲካዊ እሳቤ ጠንሳሾች ሁለቱም አካላት የስውር ተልዕኳቸው ማስፈፀሚያ ወርቃማ አጋሰሶች ናቸው፡፡ለዚህ ቀመር ፈጣሪዎች የሁለቱም ወገን ጫፍ የያዘ የጋሪ ፈረሳዊ የአንድ መስመርተኝነት ጭፍን አመለካከታቸው ለኳስ አበደች ጫወታው ማድመቂያ ፤ ደጋፊውም ሆነ ተቃዋሚውም እኩል አስፈላጊና የሆኑበት ለተግባራዊነቱ ያላቸው ሚና ተመጣጣኝ በመሆኑ ነው፡፡በሁለቱ አይጦች መካከል ያለው ልዩነት የስርዓቱ ተጠቃሚ የመሆንና ያለመሆን ጉዳይ ብቻ ነው፡፡ 
ደጋፊና ተቃዋሚ አይጦች ለዓላማው ማስፈፀሚያ መሳሪያ ከመሆናቸውም በላይ፣አንዱን ብሔር ከሌላው ብሔር ጋር የጎሪጥ እንዲተያይ የጥላቻ ዘር በመዝራት እርስ በርስ በማናከስ ሁለቱም የቤንዚንነት ሚናቸውን በተገቢው መልኩ እየተወጡ በመሆኑ ለስርዓቱ መደላደያ ምቹ መደብ ሆነዋል፡፡ የዚህ ክፋት ወለድ ፖለቲካዊ እሳቤ ጠንሳሾች የስልጣን ዕድሜያቸውን ለማራዘም፤ በዚህ እንካሰላምቲያ መሀል የራሳቸውን ወገን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትና የበላይነት ለማረጋገጥ በተለያዩ መስኮች በደህንነት መረብ፣በተለያዩ ትምህርት መስኮች ዕውቀታቸውን እያጎለበቱ፣በቴክኖሎጂ፣በመከላከያ ሐይል ግንባታ ወገናቸውን እያበቁ የማይነቀነቅ የአንድ ብሔር የበላይነት የነገሰበት ሰርዓት ለመገንባት እንዲያስችላቸው አይጦቹን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ እንደ ፈለጉት ይጋልቧቸዋል ያስጋልቧቸዋል፡፡ 
አይጦቹም በደመነፍስ ይጋልባሉ ሌላውን ንቃተ ህሊና የጎደለውን የማህበረሰብ ክፍል ማዘናጊያነት፣ ለግዜ መግዢያ ታክቲክነት በተቀመመላቸው መርዝ እራሳቸው ተመርዘው በዕውቀት ማነስ ዘአሊያም በጥቅም ተገዝቶ የሚከተላቸውን ተከታይ በመመረዝ ሀገራዊ የፖለቲካ መስመር ተፈላጊው አንድ ቅኝታዊ አመለካከት ሰለባ እየሆነ እንዲመጣ በሀገርቤት ባለውም ሆነ ዲያስፖራ ተብዬቀዎቹ ጋር የሚንፀባረቀው ሰሞንኛው የአይጦቹ ሁለት ጎራ የለየ የዘረኝነት መንፈስ ምስክር ነው ፡፡ 
ከአፄው ስርዓት ይዞ በዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ፊት አውራሪነት ይቀነቀን የነበረው የብሔር እኩልነት ጥያቄ በተሳሳተ አመለካከት ላይ እንዲገነባ፣ባለፉት ስርዓት በርግጥም ግፍ የተዋለበትን የማህበረ ሰብ ክፍል ራስህን በራስህ የማስዳደር መብት ህገ መንግስቱ አውርሶሀል በሚል ሽንገላ ከራሳቸው ጥቅም ባሻገር ለወገናቸው ህልውና ግድ የሌላቸው ሆድ አደሮችን በማቀፍ በጅ አዙር ብዙሃንን ለመርገጥና ለመጨቇን እንዲያስችል ታስቦ በሸረኞች የተቀነባበረው የፖለቲካ ጫወታ ግዜ እየጠበቀ፤ መልክና ቅርፁን እየቀየረ የሚፈነዳ ቦንብ መሆኑን እያየን ነው፡፡ዛሬ ልንክደው ልንሸፍነው በማንችለው ስፋትና መጠን ከአንድነታችን ይልቅ ልዩነታችንን እንደ ዳዊት እንድንደግም እያደረገ ያለ
የክፉዎች ክፉ ዘር ነው ፡፡ 
ለዚህም ኢህአዴግ ወደ ስልጣን ከመጣበት ግዜ አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ የተቃዋሚ ፓርቲዎች የልዩነትና ህበረት ማጣት መንስዔ፤የአንድ ብሔርተኝነት ፖለቲካዊ አጀንዳ በመሆን የለውጥ እንቅፋት ከመሆኑም በላይ በአርሶ አደሩ፣በአርብቶ አደሩ መካከል በድንበርና መሬት በተለያዩ ግዜያት የተነሱ ግጭቶች አንስቶ እስከ ፊደላውያኑ ፅንፍ ዘመምተኛ የዘረኝነት ፖለቲካ አቀንቃኞች የቃላት ጦርነት ሳይገደብ እስከ ትጥቅ ትግል መድረሱ፣በተለያዩ ወቅቶች ዩነቨርሲቲ በዘለቁ ተማሪዎች ተቃውሞና አመፅ እየታጀበ፣በተለያዩ ጎሳዎች እርስ በርስ ጦርነት ውስጥ እንዲገቡ ያደረገና እዚህም እዚያም እልቂት ያስከተለ የግፈኞች ድምፅ የሌለው መሳሪያ ነበርም እንደሆነም ይቀጥላል ዘረኝነትና የዘር ፖለቲካ፡፡የሰሞኑ የአዲስ አበባን የማስፋፊያ ማስተር ፕላን ተከትሎ በማህበራዊ ድህረ ገፆች የምንመለከተው ምልልስና ሁለት ጎራ የለየ ስሜት መራሽ አተካሮ የዘረኝነትና ጠባብነት ልካችን የት ጋር እንደ ደረሰ የሚያሳይ አሊያም አውቀንም ሆነ ሳናውቅ የፖለቲካ ጫወታው ቀመር አስፈፃሚነት አይጣዊ ሚናችን ለመወጣት ደፋ ቀና እያልን ይሆንን?!... የሚያስብል ነው፡፡

Tuesday, September 22, 2015

“ሂራር!!” አምስተኛው ቅኝት!!

ሳታውቁ በስህተት፤አውቃችሁ በድፍረት እሱ'ኮ መንግስት ሰራተኛ ነው ምትሏት ነገር አትመቸኝም፡፡...እኔ ለሀገር ነው ምሰራ (እንበል አስራ ሁለት ጊዜ)፣መንግስት በሀገር ላይ ነው የሚሰራ (እንበል አስራ ሁለት ጊዜ)...ሁለታችንም እሳት የላስን ንቦች ነን (እንበል አስራ ሁለት ጊዜ)፡፡እኔ ማር ሰራለሁ መንግስት ጠጅ ጥሎ ይጠጣል (እንበል አስራ ሁለት ጊዜ)፣ብርዝ ሰርቶ ይጨልጣል (እንበል አስራ ሁለት ጊዜ)...እኔ የማር እንጀራ ጋግራለሁ እነ እንቶኔ ሰፈፋቸውን ያንሳፍፋሉ...አረ ፍቱን-ወይ ተፋቱን (እንበል አስራ ሁለት ጊዜ)…ሂራራችንን በሰላም አስጀምሮ በሰላም ያስጨርሰን…አሜን!!! 

መንግስት ሀገር አይደለም፣መንግስት መጪና ሂያጅ ነው፣መንግስትነት አላፊ-ጠፊ ነው፡፡ሀገር ግን ዘላለማዊ ናት...እኔ ለሀገር ነው ምሰራ፣በሀገሬ ላይ ነው ምሰራ...የመንግስት ሰራተኛ ብሆን፣ለመንግስት የምሰራ ቢሆን ለምን ከእጅ ወደ አፍ ኑሮ ኖራለሁ?!...ለምን ሿሚ-ተሿሚ አልሆንኩም?!...ለምን የልማት አርበኛ አልተባልኩም?!...ለምን ሞዴል አውርቶ አደር አልተባልኩም?!...ንገሩኛ?!...የምን ስም ለጥፎ ዝም ነው?!...መልሱልኝ እንጂ?!... ለሀገር የሰራ እንጂ የመንግስት ሰራተኛ ታሪክ የለውም ... የመንግስት ሰራተኛ ከመንግስት ጋር ያልፋል፣ለሀገሩ የሚሰራ ግን ከሀገሩ ጋር ዘላለማዊ ሆኖ ይኖራል፡፡ካላጣችሁት ቋንቋ የመንግስት ሰራተኛ የምትሏት መጠሪያ፤ ስንዴውን ከንክርዳዱ ባንድ ቁና መስፈሪያ…ካንድ ስልቻ መክተቻ ተውላጠ ስማችሁ አትመቸኝም፡፡ 

አቦ አትዶክኩና!!... እስቲ እናማርበት?!...እኔ ወር ሙሉ ተጠግርሬ፣ደመወዝ ወጣ አልወጣ ብዬ...ወር ደረስኩ አልደረስኩ ስጋት እያንጠራወዘኝ...ምኑን ከምኑ እንደማረገው ቅጣምባሩ እየጠፋኝ እንደ እርጉዝ ቀን እየቆጠርኩ ከማገኛት አርባ እጅ በላዩን ግብር እያገባሁ ስለምኖር…በዚያ ላይ በአምሮት ነድጄ በምጠጣት ፍልፈል ብርጭቆ ሻይ ሳይቀር አስራ አምስት እጁን በቫት እየተሞጨለፍኩ …ሻይ ሻጩ ነዳጅ ሲጨምር በሚጨምረው፣ሲቀንስ በማይቀንሰው ያንድ ፍልፈል ብርጭቆ ዋጋ ልክ በሁለት ወገን በዱልዱሙ እየተገዘገዝኩ መኖሬ እንደ ውለታ ተቆጥሮ ቢያንስ-ቢያንስ የማማረር የዜግነት መብቴ ይጠበቅልኝ?!... 

ሂራር ህገ መንግስቱን በጉልበት ለመናድ ሙከራ ዝርዝር ውስጥ የለበትም…ህገ መንግስቱ ማንም ሰው ሆኖ የተፈጠረ…በተለይ ኢትዮጲያዊ ሆኖ የተፈጠረ የሚያማርረው ነገር አያጣምና የማማረር ሰብዐዊ መብቱ በህግ ጥበቃና ከለላ ተሰጥቶታል ይላል…ሂራር የማንኛውም ከሀገሩ ሀብት ላይ ተጠቃሚ ያልሆነ ከኑሮ ወለል በታች ያለ ኢትዮጵያዊ ዜጋ የአያልፍልሽ ኑሮ እሮሯዊ ቅኝት ነው…ከፀረ ሰላም ሀይሎች…ከፀረ-ልማት ቡድኞች…አመፅና ሰላማዊ መንገድ እንደ አዋዜ እያጣቀስን እንሄዳለን ከሚሉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተርታ አያስፈርጅም…ሂራር አዲስ አዋጅ በፓርላማ የሚፀድቅበት በቡድን ተግባራዊ ሲሆን ብቻ ነው…

እስከዚያ ድረስ አቦ አትዶክኩና!!... እስቲ እናማርበት?!... አቦ ዝምበሉና የሚሰማን ባይኖርም እናማርበት?!...አዎ እቺ “የመንግስት” ምትለው ቅጥያ ትነሳልንና ለሚገባቸው ለመንግስት አደሮች (ለሆድ አደሮች) ትሁንልን...ቢያንስ-ቢያንስ ያለስማችን አትጥሩን ...የምንሰራው ለሀገር ነው...የሰራንበትን የምትከፍለን ሀገራችን ናት...መንግስት ካሼር ነው፡፡የመንግስት ተቀጣሪነት መንፈሳችን ነው የውድቀታችን ምንጭ፤እቺ ቅጥያችሁ ባመጣችው የፍርሃት ጦስ ነው አዙረው እንደጣሉት ያቴቴ መልከኛ ወሰራ ዶሮ የመንግስት አውደልዳይ አያሌዎች እንደ አሸን የፈላነው… የህሊና እርካታ እንኳ እንዳይኖረን ያደረገን...“የመንግስት” ምትለው ቅጥያ ናት የልግመታችን ፣አውቆ የመተኛት ባህሪያችን መሰረት...ምክንያቱም እኛ ኢትዮጵያውያን ለሀገር የሚሰራ መንግስት አይስጣችሁ…እቺ ሀገር ለወገን አሳቢ ለሀገርና ህዝብ ተቆርቋሪ አይውጣብሽ “ጥቁር ውሻ ውለጂ!!” የሚል እርግማን አለባት መሰለኝ...ለመጪው ትውልድ፣ለታሪክ አስቦ የሚሰራ ቀናዒ ስርዐት አልታደልንም...አልታደለችም፡፡ 

የዚህች አገር መፃኢ ዕድል ቀን ተሌት ሚያባትተው አንድ ወዳጄ የነገረኝን ፤የመንግስት ሰራተኝነት መንፈስ የወለደው በአንድ ክልል መስሪያ ቤት የተፈፀመን ጉድ ላጫውታችሁ...ለኔ የዘመኑ ፖለቲካዊ ስርዐት ፤የኢፍትሐዊነት፣አድሎአዊነት፣ጥቂቶችን ብቻ ተጠቃሚ ያደረገ መንግስታዊ መዋቅር የፈጠረው፤ የአመለካከት ንቅዘት ውጤት ነው ባይ ነኝ...በኤክስፐርቱ፣በምሁርነኝ ባዩ ፤የአንጎል ተከፋይ በሆነው ውቅረኛ ንቀት ሰለባ የሆነው፣ጉልበት ሸጦ ማደር ኩነኔ ሆኖበት የጉልበታሙ በትር ሁሌም የሚያርፍበት “የበታች ሰራተኛው” መደብ ክፍል …ሁሌም የችግሩ ገፈት ቀማሽ የሆነው ሰራተኛ… ያባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ ተረት አዳማጭ መሆኑ ሚቆረቁረው…ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል ተረት አራማጅ ሹመኞች የበይ ተመልካች መሆኑ እንቅልፍ የነሳው የሰራተኛ ክፍል… እኔስ ከማን አንሼ ባይነት የተፈፀመ …የመንግስት ሰራተኝነት መንፈስ የወለደው ድርጊት ዛሬ ሀገራዊ አስተሳሰብ ቅኝታችን የት እንደደረሰ ማሳያ ነው ባይ ነኝ… 

ጉዳዩ እንዲህ ነው በዚህ መስሪያ ቤት ለሀገር የሚሰሩ ዜጎች በተለያዩ መንገዶች በደል ይደርስባቸዋል፡፡በብሔራቸውና በፖለቲካ አመለካከታቸው ተገለው የበይ ተመልካች መሆናቸው ሁሌም እንደ እግር እሳት ያንገበግባቸዋል፤ በተለይ ጥጉው ሰራተኛ…ምክንያቱም ወዶም ይሁን ተገዶ፣አሊያም ለመኖር ሲል የሚያፎደፉደው ሰራተኛን አፍ ማዘጊያ ጥቅማ-ጥቅም እንዲያገኝ በስብሰባ፣በስልጠና፣በመስክ ስራ ወዘተ የተጋነነ አበል እንዲያገኝ ይደረጋል...በዚህ አይነት አሰራር …የእከከኝ ልከክህ ሰንሰለት…የበልተህ አብላኝ መዋቅር…እንዳያማህ ጥራው እንዳይበላ ግፋው ፍልስፍና ተጠቂዎች…በዚህ ለመንግስት አደርነት ወረርሽኝ ባመጣው ግለኝነትና ራስወዳድነት ከጥቅም ውጭ የተደረጉት የበታች ሰራተኞች ታዲያ እጃቸውን አጣጥፈው አልተቀመጡም...ሁሉም የድርሻዬን በየት በኩል ልንጠቅ እያለ መላ ይዘይዳል …ሁሉም በቻለው መንገድ ተጠቃሚ ለመሆን ያሴራል…ባገኘው አጋጣሚ የሀገርና ህዝብ ገንዘብ ለመቦጥቦጥ የሚያደባ ተኩላ ጥሩ አድርጎ የሌብነት ሀሁ አስጠንቶታል… በማን ይፈረዳል ነገሩ የአሳ ግማቱ ከወደ አናቱ አይደል…

 የሰው ልጅ መቼም ምንም ቀለም ቢገባውም ባይገባውም…አስኳላ ቢዘልቅም ባይዘልቅም ለተንኮልና ለጥፋት ተፈጥሮው ትበቃዋለች፡፡ ታዲያ በዚህ የመንግስት መስሪያ ቤት የሚገኙት የጥበቃ ሰራተኞች እነሱም የድርሻቸውን ከሀገራቸው ላይ የሚቦጠቡጡበት በር ሁሉ ቢከረቸምባቸው ፊታቸውን በመስሪያቤቱ ውስጥ ወደሚገኙት የሚያማምሩ ዕድሜ ጠገብ ዛፎች ያዞራሉ…ለሊት-ለሊት ጥበቃ ሲያድሩ በማያስነቃ መልኩ ዛፎቹን በቁማቸው እንዲደርቁ ስራቸውን በዘዴ በመበጣጠስ… ላይን በማይታይ ሁኔታ በስለት ግንዳቸውን እየወጉ በማድማት ቀስ በቀስ እንዲደርቁ ያደርጋሉ…በመስሪያ ቤቱ ያልተጻፍ ህግ መሰረት ዛፎች ሲደርቁና ቅርንጫፎቻቸው ሲያስቸግሩ የጥበቃ ሰራተኞች ዛፎቹን ለመቁረጥ የሚያወጡት ጉልበት ታሳቢ ተደርጎ ካትክልተኞች ጋር የማገዶ ቅርጫ እንዲገቡ ማድረግ የተለመደ ነው፡፡ ይሄ ባብዛኛው አለቃ ዘንድ የበታች ሰራተኞችን እንደ አፍ ማዘጊያ ጥቅማጥቅምም የሚቆጠር ነው…አንዳንዴም ደፈር ያለ የጥበቃ ሰራተኛ ሲመጣ ከዚህ በኋላ ማገዶውን በጨረታ እንሸጠዋለን እያሉም ያስቦካኩበታል …አንዳንድ በጠመንጃ የሚጠበቅ የመንግስት መስሪያ ቤት ጥበቆች ከአለቆቻቸው ጋር ሲዋገሙ “እኔ የከፋኝ ሰው ነኝ ደፍቼው እጄን ለመንግስት ሰጣለሁ” እያሉ ስለሚዝቱ ማገዶው አትወስድም ማለት ለአብዛኛው ሹመኛ የማይሞከር ነው… 

ታዲያ ዛፍ ከደረቀ በኋላ ባለቅርጫዎቹ በፊርማቸው የተስማሙበት በግቢው ውስጥ ያለውን የደረቀ ዛፍ (ምክንያቱ አይጠቀስም)ቆርጠን እንውሰድ ጥያቄ የያዘ ደብዳቤ በጥበቃ ጓድ መሪያቸው አማካኝነት ለአለቃው ይቀርባል፡፡ለተፈፃሚነቱ የአለቃው ትዕዛዝ ተዋረዱን ጠብቆ፣የስልጣን ሰንሰለቱን ማዕከል አድርጎ …ህጋዊ መሰረት እንዲይዝ ተደርጎ የማገዶ ቅርጫ ክፍፍሉ ተግባራዊ ይደረጋል …በዚህም ሰራተኞቹ ከሀገራቸው ሀብት ላይ የበኩላቸውን ተጠቃሚነት ያረጋግጣሉ፡፡ ይኼ ባንድ መስሪያ ቤት ውስጥ እየተፈፀመ ያለ ድርጊት መልክና ቅርፁን ቀይሮ በሌሎችም ቦታዎች ስላለመደረጉ ዋስትና የለንም፡፡ ምክንያቱም በዚህ ሴራ፣በዚህ የነቀዘ አመለካከት፣በዚህ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል አህያዊ አስተሳሰብ የመንግስት ሰራተኛው ከትልቅ እስከ ትንሹ እየቦካ ስለመምጣቱ ይኼ የድንቁርና ድርጊት አመላካች ነው፡፡

 መንግስት ሰራተኝነት የወለደው፣የወቅቱ ስርዐትና ፖለቲካ የፈጠረው የመልካም አስተዳደር ችግር ሀገራዊ አመለካከት ዋግ እየመታው፣ኢትዮጵያዊነት ዛሬ በልቼ ልሙት በሚል ማህበረሰባዊ ቅኝት እየተቃኘ ስለመምጣቱ፣ ስርዐት ወለድ ያመለካከት ተስቦ ወረርሽኝ ምልክት ነው፡፡ይኽ ነቀርሳዊ አመለካከት ከቤተሰብ ወደ ልጅ፣ካንድ መንደር ወደ ሌላ መንደር፣ካንዱ ክልል ወደሌላው ክልል እየተዛመተ ነገ ሀገር የሚያጠፋ ሰደድ እሳት መሆኑም አይቀርም…እየሆነም ነው፡፡

…ይኼም ሂራር ነው…ስድስተኛው እሮሯዊ ሀገርኛ ኑሮ የወለደው ሙዚቃዊ ቅኝት!! ሳታውቁ በስህተት፤አውቃችሁ በድፍረት እሱ'ኮ መንግስት ሰራተኛ ነው ምትሏት ነገር ማትመቸኝ የዚህ አመለካከት ዕድርተኞች፣ዕቁብተኞች፣ባለደቦዎች ባለወንፈሎች ጋር የምታወናፍል… ከኑግ ጋር የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ አይነት…ጅብ በበላ ዳዋ ተመታ አይነት ጅምላ ፍረጃ ብትሆንብኝ ነው…...ለምን ቢባል የመንግስት ሰራተኛ ከመንግስት ጋር ያልፋል፣ለሀገሩ የሚሰራ ግን ከሀገሩ ጋር ዘላለማዊ ሆኖ ይኖራል፡፡ካላጣችሁት ቋንቋ የመንግስት ሰራተኛ ምትሏት መጥሪያችሁ ስንዴውን ከንክርዳዱ ባንድ ቁና መስፈሪያ…ካንድ ስልቻ መክተቻ የተውላጠ ስም ታርጋችሁ በ“ሀ.ሰ.” ትተካልኝ፡፡ሂራራችንን በሰላም አስጀምሮ በሰላም ያስጨረሰን ሕገ-መንግስታችን ስሙ ይባረክ!!… በግራችሁ ለሂራር እንደመጣችሁ በባቡር ወደ ቤታችሁ ተመለሱ…አሜን!!!

Saturday, September 19, 2015

አንጀት የሚበላ ሀባሻዊ አንጀት!!



ሀበሻነቴን ያለቅጥ እወደዋለሁ፡፡ኢትዮጵያዊነቴን የምወደው ማንነቴ ብቻ ሳይሆን መደነቂያዬ፣የአግራሞቴ ምንጭ፣የመደነቅ ጥበብ ያወረሰኝ ስጦታዬ ስለሆነም ጭምር ነው፡፡ሀበሻና ሀበሻዊነት ለእንደኔ አይነቱ ለአድናቂና ተደናቂ የእውቀት፣የጥበብ፣የትዝብት፣የፌዝና የሳቅ መፍለቂያ ከመሆን በላይ ሰርክ በአድናቆት የሚወዘውዝ ሀበሻዊ መልክ፣ኢትዮጵያዊ ገፅ እና ቀለም ጋር ባንድነት ከሌላው ዓለም ሰዎች በተለየ ሁናቴ በኢትዮጵያዊ ማንነትና ሰውነት ተውቦና ተኩሎ የሚገኝባት በዚህችው እኔኑ መሽቶ በነጋ ቁጥር በምታስደምመኝ... ለድማሜ በተፈጠርኩባት፣በፈጠረችኝ ሀገር እና ወገን መሀል ስላለሁ  ይመስለኛል፡፡

የሀገሬ ሰው ብዙ ነገሩ ድንቅ ይለኛል...አንዳንዴ እግዜሩ እኔን ብቻ ነው እንዴ በትንሽ-በትልቁ፣በረባው ባልረባው አስገራሚ ሳይሆን ተገራሚ አድርጎ የፈጠረኝ እያልኩ እገረማለሁ...ሁሌም  ዓውደ-ዓመት በመጣ ቁጥር አግራሞቴን የሚጭረው ጉዳይ አንጀት የሚበላው ሀበሻዊ አንጀታችን ነው፡፡ሀበሻና አንጀት ያላቸው ትውፊታዊ፣ስነልቦናዊ ቁርኝት ከመደነቂያ ሀበሻዊ ጉዳዮቼ አንደኛው ነው፡፡ መደነቄ ቅጥ እና ወደር የለውም የምላችሁ ከልቤ ስለሚያስደንቀኝ ነው፡፡ለምን ቢሉ በምድራችን ላይ አንጀት የሚበላ፤አንጀቱም የሚበላ ህዝብ ኢትዮጵያዊ ብቻ ይመስለኛል፡፡እንዴት?!...ለምን ካላችሁ?!...ይኸው አስረጂ
               በላሽው አንጀቴን በላሽው
               በላሽው አንጀቴን በላሽው
               ሸገር አዲሳባ ሸዋ ላይ ያለሽው
እያለ በዘፈንና፣በግጥም አንጀት የሚበላና፣አንጀቱ የሚበላ ህዝብ በሌላው ዓለም ስለመኖሩ እጠራጠራለሁ፡፡ለአንጀት ልዩ ፍቅር አለው ህዝቤ፣...ለአንጀት ልዩ ስፍራ አለው ያገሬ ሰው፣...አንጀት ቅኔው፣አንጀት ሰምና ወርቁ ነው ወገኔ...አንጀት መለያው፣አንጀቱ መታወቂያው ነው ሀበሻ...ባንጀት እና ባንጀቱ ፌዝ አያውቅም...ሀበሻን ባንጀትና በሆዱ አትምጡበት...ከመጣችሁበት ግን...
               አንጀቴና ሆዴ ተጣልተውብኝ
               አንተም ተው ፣አንተም ተው እንዳልላቸው
               አንጀቴም አንጀቴ፤ሆዴም-ሆዴ ነው
ይላችኋል፡፡
ሀበሻ አንጀት ሲበላ አልቦ ነው የሚበላ...አንጀት ገምዶ፣ፈትሎ ነው የሚበላ...አንጀት አድቅቆ ነው የሚበላ...የሚበላው የሰው አንጀት ቢያጣ የከብት አንጀት በፍቅር ይበላል ያገሬ ሰው፡፡በልዩ ሀበሻዊ ጥበብ እና ብልሃቱ በቅመም አሳብዶ በቃሪያ፣በጥብስ ቅጠል፣በነጭ ሽንኩርት አቁላልቶ፣ዶልቶ...ዱለት አርጎ...አንጀት ጠብሶ፣አንጀት ለብለብ አርጎ አሊያም በጥሬው አንጀት ይበላል ኢትዮጵያዊ፡፡

ያገሬ ሰው አንጀት መብላት ያውቅበታል፡፡ሀበሻ በግ የሚያርደው ለዱለት ካለው ጥልቅ ፍቅር የተነሳ ይመስለኛል፡፡አንጀት ለመብላት ይመስለኛል፡፡ሀበሻ ዱለት ማልዶ ሳይቀምስ ቅልጥም አይቀለጥምም፣ፍሪምባና ጎድን፣ሳላይሰጥና ወርች አያምረውም፡፡ዱለት ዓውደ-ዓመት ማድመቀዊያው ነው፤...ሀበሻ በዓል-በዓል የሚሸተው የትኩስ ዱለት መዓዛ አፍንጫውን ሲኮረኩረው፣ሰርኑን ሰርስሮ ሲገባ ነው፡፡የዱለት መዓዛ ከጠጅ-ሳር፣አሪቲ፣ጤናዳም፣ከከርቤና እጣን ጢስ፣ከጠጅና ጠላው፣ከቁሌት ጋር የተደባልቆ  አየሩን ሲሞላው...ይኼን ዱለታዊ የማለዳ አየር ማግ-ማግ ሲያደርግ ነው ዓውዳመቱ ዓውዳመት የሚመ ስለው...በዓሉ በዓል የሚሆንለት፡፡
ለሀበሻ ዱለት የሌለበት በዓል ትዝታ የለውም፣ጎደሎ ነው፡፡...አንጀት የሚያቃጥል፣አንጀት የሚለበልብ፣አንጀት የሚያነድ ዓውዳመታዊ ጠባሳ ጥሎበት ያልፋል፡፡ሀበሻ በዓል፣ድግስ፣ሰርግና ተዝካር የማይለየው አንጀት ለመብላት ይመስለኛል፡፡ለዚህ ነው ኢትዮጲያውነቴ አንጀቴን የሚበላው፣አንጀቴን የሚያንሰፈስፈው፡፡

ሀበሻ ክፉ ቀኑን የሚችለው፣መከራና ስቃዩን፣በደል እና ጭቆናውን፣የመገፋት ቁጭቱን የሚያዳፍነው አንጀቱ ስር ነው፣ካንጀቱ ቀብሮ ነው፤ ባገሬ ሁሉን ቻይ አንጀት ያለው ሰው ይቀናበታል፡፡ያገሬ ሰው ሲኩራራ የዝሆን አንጀት ሰጥቶኛል ይላል፤ክፉና በጎውን እንዳመጣጡ የሚቀበልበት ሰፊ ሆድ እና ባለገበር አንጀት የሰጠውን ፈጣሪውን ተመስገን ብሎ የባሰ አታምጣ እያለ የሚኖረው ባንጀቱ ድንዳኔ እና ክሳት ልክ ነው ብሎ ያምናል፡፡ላበሻ ረጅሙ አንጀቱ የኑሮ ማሳለጫው፣ከክፉ ቀን መሰወሪያው ፣መሸሸጊያው ነው፡፡

ወገኔ የነገር መክተቻ ስልቻው፣እውነተኛ ስሜቱን መደበቂያ ጎተራው፣ክፉና ደጉን ማጎሪያ ጉረኖው አንጀቱ ነው፡፡ያገሬ ሰው የልቡን-በልቡ ያንጀቱንም-ባንጀቱ መያዝ የተካነ ዚቀኛ ነው፡፡እንኳን ለባዳ ለወዳጁም ያንጀቱን አያወጣም፣መዋደድ እንዳለ መጣላት ይመጣል ብሎ አርቆ አስቦ አንጀቱን ያርቃል፡፡ሀበሻ ሀዘን ደጁን ረግጦ፣ከቤቱ አልወጣ ቢለው...ልብና አንጀቱን ጠብስቆ ሲያብሰከስከው አንጀቴ ተላወሰ፣አንጀቴ ተንሰፈሰፈ፣አንጀቴን በላኝ ይላል የሀዘኑን ጥግ ሊገልፅ ሲፈልግ፡፡

ሀበሻ ያመነው ሲከዳው፣ወዳጄ ያለው ፊቱን ሲያዞርበት፣የኔ የሚለው ሰው ቃሉን በልቶ፣እምነቱን አጉድሎ ፣ማተቡን በጥሶ ዋሾና ቀጣፊ ሆኖ ሲያገኘው አንጀቴ ተቆረጠ፣አንጀቴ ተበጠሰ ብሎ ቅያሜውን የሚገልፀው አንጀቱን ምሳሌ አርጎ አንጀቱን ተውሶ ነው፡፡

የሀበሻ ሰው ፍቅሩ እንጂ መቼም ጠቡ አያድርስ ነው፡፡ሀበሻ መውደዱ እንጂ ጥላቻው ለጉድ ነው፡፡ሀበሻ ያቄመ እንደሁ አይጣል ነው፡፡ሀበሻ እንኳን ቂም እና ጥላቻውን ፍቅሩን መሰወሪያ ስልቻው አንጀቱ ነው፡፡ሀበሻ አንጀቱ ዋሻው ነው፡፡አንጀቱ ራስ መደበቂያው አመሉን መክተቻ አቁማዳው ነው፡፡ሀበሻ ነገር ማሰንበቻ፣ማኮምጠጪያ፣ማርጊያ አካሌ አንጀቴ ነው ይላል...ነገር ሲገባው ተው ቻለው አንጀቴን ማንጎራጎር ልማድ አለው፡፡ሀበሻ ፍቅርና ደግነቱን፣የክፋትና ጥላቻ አብሲቱን የሚጥለው፣የሚያብላላው፣የሚደፈድፈው፣የሚያፈላው ፣የሚያቀዘቅዘው ባንጀቱ ውስጥ ነው፡፡

ሀበሻ እንኳን ለወዳጁ ለራሱም ስውር ነው፡፡ወሬና ነገር ከሆዱ ማይረጋለት፣ካንጀቱ ማይቀመጥለት ሀበሻ ነውረኛ ፣ምስጢር መቋጠሪያ የሌለው ወሽካታ፣ወናፍ፣አንድ አይውል፣ ቁምነገረ-ቢስ፣ ከንቱ ተደርጎ ይብጠለጠላል፡፡ሀበሻ አንጀተ ደንዳና እንጂ አንጀተ ወንዋና፣አንጀተ ከሲታ ጥሎበት አይወድም፡፡አንጀተ ልፍስፍስ ሰው ጀግና፣ደፋር፣ጎበዝ፣ብርቱ ከሚውልበት አደባባይ አይውልም፤ ካንድ ማዕድ አይቆርስም፡፡
ሀበሻ  ደስ ሲለው፣የልቡ ሲደርስ፣ያሰበው ሲሳካለት፣የተመኘው ሲሆንለት፣ስለቱ ሲሰምርለት አንጀቴ ቂቤ ጠጣ፣አንጀቴ ራሰ ብሎ የደስታ ጥሙን የሚቆርጠው፣የእርካታ ፅዋውን የሚጨልጠው ወደ አንጀቱ ነው፡፡

ታዲያስ እኔስ ሀበሻ አይደለሁ አንጀት መብላት የለመደ ሀበሻዊ አንጀቴ አውደ-ዓመት ሲመጣ ናድ-ናድ ፣ፍርስ-ፍርስ ይልብኛል...የዘንድሮው በአል  ደግሞ ባዲስ ህዳሴያዊ ፍቅር አንጀቴን ያንሰፈስፈው ይዟል!...ተሳለጥ-ተሳለጥ ይለኛልጂቲፒ-ጂቲፒ ይለኛልተናገር-ተናገር ይለኛልቃሊቲ-ቃሊቲ ይለኛልጉባዔ-ጉባዔ ይለኛል….እንብላ-እንብላ ይለኛልእሰር-እሰር ይለኛልአሸባሪ-አሸባሪ እያለ ሽብር ይለቅብኛልፍትህ-ፍትህ ይለኛልተሰደድ-ተሰደድ ይለኛልሀገር የለህም ይለኛልአንጀቴ ስሩ ይመረኛልእልህ አንጀቴን ያስልበኛልያልሄድንበት መንገድ ጨኛልየምናወራውና ተግባራችን ፍየል ወዲህ ቅዝምዝም ወዲያ ይሆንብኛልአረ አይነጋም ወይ ያስቀነቅነኛልየጨለማ ጉዟችን ማብቂያ አልታይህ ይለኛልበመርከባችን ካፒቴኖች እንደ ውሃ ላይ ኩበት መዋለል ታክቶኛልአርበኝነት እየከሰመ ሞላጫነት እየነገሰ ሲመጣ እያየሁ የተስፋ አንጀት ርቆኛልየሚያዋጣኝ ይሄን እሳትራታዊ ሃሳብ ወዲያ ትቶ አረ-ምኑን ሰጠሽ እያልኩ መዝፈንአሊያም በዚህ አዲስ ዓመት ከቀናኝ አንድ ምኑ የተሰጣትን ባለመቀመጫ ፈልጌ ከጢዟ ስር ተደብቄ ይሄን ክፉ ቀን ማሳለፍ
ለናንተ ለወገኖቼ አውደ-ዓመት ሲመጣ የዱለት አምሮት የጠናበት፤ ሀበሻዊ ሆድና አንጀታችሁ ለሚባባ ከሀገር እና ቤተሰብ ርቃቸሁ፣የስደት ኑሮ፣የባዕድ ሀገር ህይወት አልሞላ ላላችሁ መለየትና ናፍቆት አንጀታችሁን ለሚበላችሁ፣...እናት እና አባታችሁን፣ባልና ሚስታችሁን፣ወንድምና እህታችሁን፣ፍቅረኛና ልጃችሁን ሞት ቀምቶ ሀዘን አንጀታችሁን ለሚያኝከው፣...በዘመኑ ፖለቲካ ያለወንጀላችሁ ከእስርቤት ተወርውራችሁ፣ዘብጢያ ወርዳችሁ በክፋት ጓጉንቸር ለተከረቸማችሁ፣በሆስፒታል አልጋ ላይ በህመምና  በስቃይ ላላችሁ፣ የምትወዷት ወይም የምትወዱት ልጅ ቤተሰብ ጥየቃ ሄዶባችሁ በመለየትና በብቸኝነት አንጀታችሁ ለሚላወስ እና ዱለት አልበላ ላላችሁ፣ለከፋችሁም-ደስ ላላችሁም፣ለሞላላችሁም-ለጎደለባችሁም...ለትንሾቹም ለትልቆቹም...ለእናንተ ለወገኖቼ ለሁላችሁ አንጀት ሚወደው፣ዱለት ያማረው ሀበሻዊ አንጀቴ እስኪላወስ እወዳችኋለው...መልካም አዲስ-ዓመት ይሁንላችሁ፡፡